የቤተክርስቲያኗ ታሪክ | History

የኆኅተ ምሥራቅ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን በጥቅምት 1 ቀን 2004 ዓ.ም (November 9, 2011) በሲልቨር ሰፕሪንግ ሜሪላንድ: አድራሻው 8900 Georgia Ave, Silver Spring, MD 20901 ንብረትነቱ የሌሎች ቤተ እምነት በሆነው ሕንጻ አዳራሽን በመከራየት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ መምህራን፣ ዘማሪያን፣ የሰንበት ት/ቤት አባላት እንዲሁም ምዕመናን እና ምዕመናት በተገኙበት በብፁዕ አቡነ አብርሃም ቡራኬ ተመሰረተ።ቀድሞ በቨርጂንያ ግዛት በሀገረ ስብከቱ ሥር ተተክሎ ከነበረው የምሥራቀ ፀሓይ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የሰበካ ጉባኤ አስተዳደር ጋር በመመካከር በአገልጋይ ካህናትም ሆነ በምእመናን ዘንድ ቅሬታ ሳይፈጠር የአገልጋይ ካህናት እጥረት ስለነበር የአገልግሎት ክፍተት እንዳይፈጠር በማሰብ ያሉትን ካህናት በአግባቡ ለመጠቀም የኆኅተ ምሥራቅ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ቅዳሜ እንዲሆን ተደረገ።
ቤተ ክርስቲያኒቱ ጀማሪ እንደመሆንዋ የራስዋን ነዋየ ቅድሳት እስክታሟላ ድረስም ከምሥራቀ ፀሓይ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ነዋየ ቅድሳት በማምጣት ነበረ አገልግሎት የተጀመረው። ይህ ዓይነቱ መተባበር በአንዲት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም በተመሠረቱ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ሊኖር የሚገባ እንደልዩ ነገር ሆኖ ተጋኖ ሊነገር የማይገባ መሆኑ የታወቀ ነው ዳሩ ግን እንደ አለመታደል ሆኖ በውጭው ዓለም አብዛኛዎቹ አብያተ ክርስቲያናት በፀብ፣ በጥላቻ የተመሠረቱና የሚመመሰረቱ በመሆኑ እንኳን ካህናትንና ነዋየ ቅድሳትን ተጋርተው ሊያገለግሉ የአንዱ አጥቢያ ምእመን ወደ ሌላኛው አጥቢያ ዝር እንዳይል የፀብ ግድግዳ ነው የሚገነባው።የኆኅተ ምሥራቅ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን፤በፀብና በጥላቻ ያልተመሠረተ፤ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በጠበቀ መልኩ ከተቋቋሙት አብያተ ክርስቲያናት አንዷ በመሆንዋ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን።
ቅዳሜ ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ አራት ሰዓት(6:00am 10:00am) የነበረው አገልግሎት ለሰባት ወራት ያህል ከቆየ በኋላ ምእመናን እየበዙ አገልግሎቱም እየሰፋ በመምጣቱና አገልጋይ ክህናትም በመብዛታቸው፤ቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎቷን በማጠናከር ከ ሰኔ 3፣ 2004 ዓ/ም ( June 10, 2012) ጀምሮ ዘወትር እሁድ ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ 5 ሰዓት (6 am – 11 am ድረስ) (7700 Carol Ave,Takoma Park, MD 20912) በሚገኘው የስላይጎ አድቬንቲስት ቸርች ቦታ በመከራየት አገልግሎቱ ተጠናክሮ ቀጠለ።
ሥራው ድንቅ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር በቅድስት እናቱ አማላጅነት ረድቶን ቤተ ክርስቲያኑ በተመሰረተ በአጭር ጊዜ በጥር 25, 2008 ዓ.ም(Feb.3, 2016)በሜሪላንድ ግዛት በሃይትስቪል ከተማ አድራሻው 6509 Riggs Road,Hyattsville MD 20782 የሆነውን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በ2.5 ሚሊዮን ዶላር ለመግዛት በቅቷል። የራሳችን የሆነ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን እንዲኖረን በማድረግ ትልቁን ድርሻ የወስዱት የአጥቢያው የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ፣ የደብሩ ካህናት፣ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎችና ምእመናን ምንግዜም ሲዘከር የሚኖር አኩሪ ታሪክ ፈጽመዋል::
የኆኅተ ምሥራቅ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን በዋናነት መሠረት ያደረገችው ትውልድን መታደግ በሚለው መርህ ላይ በመሆኑ እዚህ ሀገር የተወለዱትንና ያደጉትን ትውልደ ኢትዮጵያውያን ላይ ትኩረት በማድረግ እድሚያቸውን መሠረት በማድረግ የተዘጋጀን ሥርዓተ ትምህርት በመጠቀም ልጆች የቤተ ክርስቲያናቸውን መሰረተ እምነትና ሥርዓት እንዲያውቁና የነገይቱን ቤተ ክርስቲያን እንዲረከቡ ማድረግ የቤተ ክርስቲያኒቱ ዓላማና ግብ ነው።
Hohte Misrak Kidane Mihret Ethiopian Orthodox Tewahido Church (HMKMEOTC) is a non-profit organization tax exempt under IRC 501(c) (3) rules of IRS. The HMKMEOTC belongs to the ancient, Apostolic Oriental Orthodox Churches that maintain the teachings and practices of the Holy Tradition of One, Holy, Apostolic Church founded by Our Lord Jesus Christ. We are a place where people can unite to worship God as one family – regardless of ethnic, cultural or spiritual background.